የአማራ ክልል አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግ ለህግ ታራሚዎች ይቅርታ አደረገ፡፡
የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት መስተዳድር ምክር ቤት ነሐሴ 29 ቀን 2009 ዓ.ም ባካሄደው 5ኛ ዙር ሦስተኛ ዓመት የሥራ ዘመን 1ኛ አስቸኳይ ስብሰባ የ2010 ዓ.ም የዘመን መለወጫ በዓልን ምክንያት በማድረግ ለ1 ሺህ 981 የህግ ታራሚዎች ይቅርታ ማድረጉን ገለፀ።
ይቅርታ የተደረገላቸው ታራሚዎችም የወንጀልን አስከፊነት የተገነዘቡና ከወንጀል ድርጊት ለመታረም ያላቸውን ዝግጅት በመመዘን የይቅርታ መስፈርቱን ያሟሉ ሲሆኑ፣ ወደ ህብረተሰቡ ሲቀላቀሉ ሰላማዊና አምራች ዜጋ እንዲሆኑ ማድረግ እንደሚገባም ተናግረዋል።
በውጭ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የቤት መስሪያ ቦታ አሰጣጥ ማሻሻያ ረቂቅ ላይ ውሳኔ መሰጠቱ ተገለጸ፡፡ በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት መስተዳድር ም/ቤት 5ኛ ዙር 3ኛ አመት የስራ ዘመን ነሀሴ 19/2009 ዓ/ም ባደረገው 4ኛ መደበኛ ስብሰባ በውጭ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ አሰጣጣጥ ማሻሻያ ረቂቅ መመሪያ ላይ ተወያይቶ ውሳኔ መሰጠቱ ተገለጸ፡፡ ስብሰባው የተጀመረው የከተማ ልማት ቤቶችና ኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ ባቀረቡት ማብራሪያ ሲሆን በውጭ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን በማህበር ተደራጅተው የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ ለማግኘት የሚያስችላቸው መመሪያ ቁጥር 22/2007 ዓ/ም በመስተዳድር ም/ቤቱ የወጣ ቢሆንም እስከ አሁን ድረስ ጥያቄ ያቀረቡና የመመሪያውን መስፈርት አሟልተው የተመዘገቡ ዳያስፖራዎች እንደሌሉና ለመመዝገብ ዋናው ምክንያትም በመመሪያው ላይ የተቀመጡትን የቤት አይነቶች የግንባታ ወጭ ቅድሚያ 100% በመክፈል በዝግ አካውንት በባንክ ለማስቀመጥ አቅማችንን ያገናዘበ ባለመሆኑ ይሻሻልልን የሚል ጥያቄ ያላቸው በመሆኑ ቢሮው ከዳያስፖራ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ዳይሬክቶሬት ጋር በጋራ በመነጋገር መመሪያው ላይ ማሻሻያ ተደርጎ የቀረበ መሆኑን ገልጸው ማሻሻያው በዋናነት ከክፍያና ከቦታ መጠን ጋር የተያያዘ እንደሆነ አብራርተው ማሻሻያው እንዲጸድቅላቸው ጠይቀዋል፡፡ መስተዳድር ም/ቤቱም በቀረበው ጉዳይ ላይ የተለያዩ ሀሳቦችን በማንሳት በሰፊው ከተወያየ በኋላ በወጣው መመሪያ ላይ አላሰራ ያሉ ችግሮችን ፈትሾ ማሻሻያ ማድረግ ተገቢ በመሆኑ የቀረበው በውጭ ሀገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ አሰጣጥ ማሻሻያ ረቂቅ መመሪያ በቀረበበት መልኩ ተሻሽሎ ተግባራዊ እንዲደረግ ወስኗል፡፡
የሶማሊያ አገር ከፍተኛ አመራሮችና የምክር ቤት አባላት በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ርእሰ መዲና ባህርዳር በፌዴራሊዝም ስርዓት ዙሪያ የልምድ ልውውጥ አካሄዱ፡፡ ከጎረቤት አገር ሶማሊያ ከፍተኛ አመራሮችና የምክር ቤት አባላት ጋር የተካሄደውን የልምድ ልውውጥ በንግግር የከፈቱት የአማራ ብሄራዊ ክልል ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ የተከበሩ አቶ ይርሳው ታምሬ እንደገለፁት አገራችን ኢትዮጵያ ላለፉት 25 ዓመታት በፌዴራሊዝም ስርዓት ቆይታለች በዚህም የህዝቦችን መፈቃቀር፤ የህዝቦችን የመልማት ፍላጎትና አቅም ለማጠናከር በመቻላችን አገራችን በልማት ፈጣን እድገት እያስመዘገቡ ከሚገኙ ሃገራት መካከል አንዷ ልትሆን ችላለች ብለዋል፡፡ እንደ አቶ ይርሳው ገለፃ በፌዴራሊዝም አወቃቀር ከተደራጁ ክልሎች መካከል አንዱ የሆነው የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በሃገሪቱ የኢኮኖሚና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ውስጥ ጉልህ ድርሻ ያለው ክልል ነው፡፡ በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ርእሰ መስተዳድር ፅ/ቤት በቢሮ ኃላፊ ደረጃ የርዕሰ መስተዳድሩ ከፍተኛ የህግ አማካሪ አቶ መርሃ ፅድቅ መኮንን እና የክልሉ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ትብብር ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ጥላሁን መሓሪ ክልሉ ያለበትን አጠቃላይ ደረጃ የሚገልፅ ጽሁፍ ቀርቦ ውይይት የተደረገበት ሲሆን ከጎረቤት አገር ሶማሊያ ከፍተኛ አመራሮችና የምክር ቤት አባላት ጥያቄዎች ቀርበው ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ በጎረቤት አገር ሶማሊያ የሃገር ውስጥ ሚኒስትርና የፌዴራሊዝም ቋሚ ሚኒስትር ሴክሬታሪያት እንዲሁም የልዑካን ቡድኑ መሪ አቶ አብዱላሂ መሃመድ ሁሴን እንደገለጹት ባጠቃላይ በፌዴራሊዝም ስርዓት ውስጥ በህግ አውጭው፤ በህግ ተርጓሚው፤ በህግ አስፈጻሚው የአሰራር ስርዓት ዙሪያና እንዲሁም የፌዴራሊዝም ስርዓት ለብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች እኩልነትና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ያለውን ጠቀሜታ ለመረዳት ችለናል በመሆኑም ለኢትዮጵያን መንግስትና የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ምስጋናችንን ከፍተኛ ነው ብለዋል ፡፡
በመጨረሻም የልዑካን ቡድኑ አባላት በባህር ዳር ከተማ የተለያዩ የልማት ስራዊችን ጎብኝተው ወደ አገራቸው ተመልሰዋል፡፡ |
የርዕሰ መስተዳድር ጽ/ቤት ሠራተኞችና አመራሮች በኤች.አይ.ቪ/ኤድስ እና በወቅታዊ የበሽታው ስርጭት ዙሪያ ውይይት አደረጉ፡፡
ነሐሴ 18/2009 ዓ.ም በአማራ ክልል የርዕሰ መስተዳድር ጽ/ቤት ሠራተኞችና አመራሮች ኤች.አይ.ቪ/ኤድስ ያለበትን ደረጃ በተመለከተና በወቅታዊ የበሽታው ስርጭት ዙሪያ ውይይት ማድረጋቻው ተገለጸ፡፡
በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ጤና ቢሮ የኤች አይ ቪ/ኤድስ ዘርፈ ብዙ ምላሽ ማስፋትና ማጠናከር ባለሙያ አቶ መልካሙ ዳኛው እንደገለጹት የቫይረሱን ስርጭት ለመከላከል የሚደረገው እንቅስቃሴ ተቀዛቅዟል፡፡ በዚህም በሽታው ጠፍቷል በሚል ደረጃ መዘናጋት እየተፈጠረ ሰዎች ወደ ስህተት እየገቡ ነው፡፡ የቫይረሱ ስርጭት የመቀነስ አዝማሚያ ቢያሳይም አንዳንዶቹ ጠፍቷል በሚል ልቅ ወሲባዊ ግንኙነት በመፈጸም የቫይረሱን ስርጭት እንደገና በከፍተኛ ሁኔታ እንዲያገረሽ እያደረጉት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ በተለይ የትራንስፖርት ኮሪዶር በሚባሉ ታላላቅ ከተሞች የተጠናን የጥናት ውጤት መነሻ በማድረግ የቫይረሱ ስርጭት ከፍተኛ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ለአብነት ምንጃር ሸንኮራ 4.5%፣ምዕራብ አርማጮሆ 4.4%፣ባህር ዳር 3.7%፣ደቡብ አቸፈር 3.1% የስርጭት መጠን እንዳላቸው አብራርተዋል፡፡ በጥናቱ ከተካተቱ ከተሞች መካከል በሴተኛ አዳሪዎች ደረጃ ይበልጥ ተጋላጭ በሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ያለው የስርጭት ሁኔታ አስደንጋጭ ውጤት የተመዘገበው በባሕር ዳርና በኮምቦልቻ ከተሞች ሲሆን በጥናቱ መሰረት በባሕር ዳር 32%፣ በኮምቦልቻ ደግሞ 29% ሴተኛ አዳሪዎች በደማቸው ውስጥ ኤች.አይ.ቪ/ኤድስ ያለባቸው መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ የአገራችንን ልማት ለማፋጠን ዋነኛው የሰው ሀብት ልማት ከመሆኑ አንጻር ኤች.አይ.ቪን መግታት የልማቱ ኃይል የሆነውን ህብረተሰብ መታደግና ጤንነቱን መጠበቅ ከልማቱ ተነጥሎ የሚታይ ጉዳይ አይደለም፡፡ በመሆኑም የቫይረሱን ስርጭት ለመከላከል ሁሉም ሴክተር መስሪያ ቤቶች የኤች.አይ.ቪን መከላከልና መቆጣጠር ፕሮግራምን እንደ መደበኛ ስራ በማቀድ መስራት፣በጀት መመደብ፣አፈጻጸሙን መገምገምና ጉዳዩን የጋራ ማድረግ የሚገባቸው መሆኑን አቶ መልካሙ አመልክተዋል፡፡ በሌላ በኩል የተላላፊ በሽታዎች ክትትል ባለሙያ የሆኑት አቶ ተክለ ኃይማኖት ስለ አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት/አተት/ ምንነት የመወያያ ጽሁፍ አቅርበዋል፡፡ አቶ ተክለ ኃይማኖት እንደገለጹት አተት ከተቅማጥ በሽታዎች ውስጥ አንዱ ሲሆን፣ በአይን በማይታዩ ተሕዋስያን የሚመጣ በሽታ ነው፡፡ በመሆኑም በፍጥነት በመዛመት በአጭር ጊዜ ውስጥ ለሞት ሊዳርግ የሚችል በሽታ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የአተት በሽታ ዋናው ምልክት በድንገት የሚከሰት ብዛት ያለው አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት ሲሆን አተት ጠቃሚ ንጥረ ነገሮችንና ፈሳሽን በተደጋጋሚና አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት ስለሚያስወጣ የሰውነት ፈሳሽንና ጠቃሚ ንጥረ ነገሮችን መጠን ያዛባል፡፡ በመሆኑም የሰውነት ድርቀት፣ የአፍ መድረቅ፣ የአይን መሰርጎድ፤ የእንባ መድረቅ፤ የሽንት መቀነስ፣ የቆዳ መሸብሸብና፣ የእግር መቀረጣጠፍ፣ አጠቃላይ የሆነ የድካም ስሜት ያስከትላል ብለዋል፡፡ ይህን የአተት በሽታ ለመከላከል በውሃ ማከሚያ መድሃኒት የታከመ ውሃ መጠቀም፣ ምግብን በሚገባ አብስሎ በትኩስነቱ መመገብ፣ የምግብ ዕቃዎች ንጽህና መጠበቅ፣ መፀዳጃ ቤትን በአግባቡ መጠቀም፣ እጅን በወሳኝ ወቅቶች በሣሙና በሚገባ መታጠብ፣ ማናቸውንም ከቤት የሚወጣ ደረቅ ወይም ፈሳሽ ቆሻሻ ውሃን እንዳይበክል በአግባቡ በተመደበለት ስፍራ ማስወገድ፣ በዚህ በሽታ የተያዘ ሰው በፍጥነት ወደ ሕክምና ተቋም መዉሰድ እና ከበሽተኛው ከሚወጣ ፈሳሽ ጋር ንክኪ ያላቸውን እቃዎችና ቦታዎችን በአግባቡ ማጽዳት ሲሆን እነዚህን የመከላከያ መንገዶችን ተግባራዊ በማድረግ የአተትን መተለለፊያ ሰንሰለት ማቋረጥ ይቻላል በማለት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ የርዕሰ መስተዳድር ጽ/ቤት ሠራተኞችም በቀረበው ጽሁፍ ላይ አስተያየቶችን ሰጥተዋል፣ጥያቄዎችንም አቅርበው በባለሙያው ምላሽ ተሰጥቷቸዋል፡፡ ነሀሴ 18/2009 ዓ.ም የዳያስፖራና ህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት የሀሰተኛ የትምህርት ማስረጃ ማጣራትን በተመለከተ የተደረሰበት ደረጃና ውሳኔ የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ላይ ውሳኔ መሰጠቱ ተገለጸ፡፡ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት መስተዳድር ምክር ቤት 5ኛ ዙር 3ኛ አመት የስራ ዘመን ሐምሌ 21 ቀን 2009 ዓ/ም ባካሔደው 2ኛ መደበኛ ስብሰባ በክልሉ ውስጥ ሀሰተኛ የትምህርት፣ የመንጃ ፈቃድ፣ የስራ ልምድና የብቃት ማረጋገጫ ማስረጃዎች ማጣራትን በተመለከተ የተደረሰበት ደረጃና ውሳኔ የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ላይ ውሳኔ መስጠቱን ገለጸ፤ ውይይቱ የተጀመረው የስቪል ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ አወቀ እንየው ባቀረቡት ማብራሪያ ሲሆን፤ በማብራሪያቸውም በሥነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን በኩል በተጠናው ጥናት መሰረት በክልሉ ውስጥ ሀሰተኛ የትምህርት፣ የመንጃ ፈቃድ፣ የስራ ልምድና የብቃት ማረጋገጫ ማስረጃዎች መኖራቸው በመረጋገጡ በተደራጀ መልክ እርምጃ ለመውሰድ ያስችል ዘንድ የክልሉ መስተዳድር ምክር ቤት መመሪያ ማውጣቱን ገልጸዋል፡፡ እንደ ምክትል ኃላፊው ገለጻ በመመሪያው መሰረት በመጀመሪያው የይቅርታ ምዕራፍ ከሰኔ 15 እስከ ሐምሌ 14 ቀን 2009 ዓ.ም ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ሰራተኞችና ኃላፊዎች ራሳቸውን የሚያጋልጡበት ጊዜ ሲሆን ይህንን ጊዜ በመጠቀም 468 የክልሉ የመንግስት ሰራተኞች ራሳቸውን ማጋለጣቸውንና በመመሪያው መሰረት እርምጃ የሚወሰድ መሆኑን፤ እንዲሁም በሁለተኛው ምዕራፍ ማለትም ከሐምሌ 15 እስከ ነሐሴ 14 ቀን 2009 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ በጥቆማ መልክ መረጃ ለማሰባሰብ የሃሳብ መስጫ ሳጥንና ነጻ የስልክ መስመር አገልግሎት የተዘጋጀ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህ መሰረት በመጀመሪያው ምዕራፍ ራሳቸውን ሲያጋልጡ በነበረበት ወቅት ብዙዎቹ በመጨረሻው ቀን የመጡ በመሆኑ ከዚህ በመነሳት ራስን ለማጋለጥ የተሰጠው ቀነ ገደብ ቢራዘም የበለጠ ተነሳሽነት ይኖረዋል የሚልና በሌላ በኩል ደግሞ ጊዜው በተራዘመ ቁጥር መዘናጋትን ሊፈጥር ስለሚችል መራዘም የለበትም የሚል ሃሳብ እንዳለና፣ በሌላ በኩል ደግሞ ቋራና ሳሃላ ወረዳዎች በተለያየ ምክንያት መረጃው ዘግይቶ ስለደረሳቸው የመጀመሪያውን የይቅርታ ጊዜ መጠቀም ስላልቻሉ መራዘም የሚችልበት ሁኔታ እንዲመቻች የቀረበ ጥያቄ በመሆኑ መስተዳድር ምክር ቤቱ በቀረቡት ጉዳዮች ላይ መክሮ አቅጣጫ እንዲያስቀምጥ ጠይቀዋል፡፡
መስተዳድር ምክር ቤቱ በቀረቡት ሃሳቦች ላይ የተለያዩ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን በማንሳት ሰፊ ውይይት ካካሄደ በኋላ የሀሰተኛ የትምህርት ማስረጃ ይዘው ያለአግባብ እየተጠቀሙ ያሉ የክልሉ ሰራተኞችና አመራሮች በተደራጀ መንገድ እርምጃ ለመውሰድ እየተካሄደ ባለው እንቅስቃሴ የመጀመሪያው የይቅርታ ምዕራፍ ለተወሰነ ጊዜ እንዲራዘም የቀረበውን ሃሳብ በተመለከተ የተጀመረውን ሥራ ተጨማሪ ጊዜ ሰጥቶ ማራዘም ሳያስፈልግ ግብረ-ሃይሉ ባስቀመጠውና በክልሉ መስተዳድር ምክር ቤት ውሳኔ መሰረት መቀጠል እንዳለበት፤ በሌላ በኩል ደግሞ ከመጀመሪያውም ቢሆን በተለያየ ምክንያት መረጃው ዘግይቶ የደረሳቸው ቋራና ሳሀላ ወረዳዎች ለሌሎች የተሰጠውን የይቅርታ ምዕራፍ ጊዜ መጠቀም ስላለባቸው መረጃው ከደረሳቸው ቀን ጀምሮ ያለው ጊዜ ተይዞ ለሌሎች የተሰጠውን የመጀመሪያውን የይቅርታ ምዕራፍ ጊዜ ያህል እንዲጠቀሙ እንዲደረግ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ |